Quantcast
Channel: Amharic News & Opinion
Viewing all articles
Browse latest Browse all 13695

ዴር ሡልጣን፡- ዐሥር ነገሮች

$
0
0
ከ ሁለት ሺ ዓመታት በፊት በኢትዮጵያዊው ጃንደረባ የተገለጠው ኢየሩሳሌምን ለመሳለም የሚደረገው ጉዞ ዛሬ የሺዎች ጉዞ ሆኗል፡፡ በእግር ተጉዘው ኢየሩሳሌም ለመድረስ ሱዳንን፣ ግብጽና የሲና በረሃን ያቋርጡ የነበሩት፤ ያለበለዚያም በመካ በኩል ተሻግረው በዮርዳኖስ በኩል ይገቡ የነበሩት አባቶቻችን ክብር ይግባቸውና፣ በኢየሩሳሌም ያቆዩትን ቦታ ለመሳለምና የትንሣኤ በዓልንም በትንሣኤው ቦታ ለማክበር ኢትዮጵያውያን ከሰባ ሺ ብር በላይ እየከፈሉ ይጓዛሉ፡፡
ከዛሬ ሃምሳ ዓመት በፊት የኢትዮጵያውያን ምእመናን የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት በአዲስ መልክ የኢየሩሳሌምን ጉዞ ሲጀምር በአንድ ድርጅት ብቻ ይከናወን የነበረው ጉዞ፣ ዛሬ ከሃያ በላይ በሚሆኑ አጓጓዦች በኩል ከመላው ዓለም ኢትዮጵያውያን ይሰባሰባሉ፡፡ ከሃምሳ ዓመታት በፊት ከኢትዮጵያ በሚመጡ ተሳላሚዎች የተጀመረው ጉዞ ዘንድሮ ከ27 ሀገሮች በመጡ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ወደሚከናወንበት ደረጃ ደርሷል፡፡ ከዓመታት በፊት በአብዛኛው በሽማግሌዎችና በእናቶች ብቻ ይደረግ የነበረው ጉዞ ዛሬ ከሦስት ወር ጽንስ እስከ 94 ዓመት አዛውንት ተካትተውበት የሚደረግ ሆኗል፡፡
ከዐሥር ዓመታት በፊት የትንሣኤ በዓል በዴር ሡልጣን ሲከበር በአንደኛው የገዳሙ አጥር ጥግ ተሰባስበው ይታዩ የነበሩት ተሳላሚዎች ዛሬ ግቢው ጠቧቸው፣ መንገዶችን አጨናንቀው፣ ጠጠር መጣያ እስከ ማሳጣት ደርሰዋል፡፡ ወይም አንድ የእሥራኤል ጋዜጠኛ እንዳለው ‹‹ነጭ ጎርፍ በፍኖተ መስቀል በኩል ሲፈስ የሚታይበት ተአምር›› ላይ ደርሰዋል፡፡ ድንበር የለያያቸው ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ዜግነት ሳያግዳቸው፣ ሃይማኖት አገናኝቷቸው በአንድ የሚያመልኩበት፣ አንድ ማዕድ የሚቆርሱበት፣ የዘመድ ወግ የሚያወጉበት ሥፍራ ሆኗል፡፡

ይህ ሁሉ እግዚአብሔር የሰጠን ዕድል ቢሆንም ከተጠቀምንበት ነገር ያልተጠቀምንበት ይበልጣል፡፡ የዚህ ዋነኛ ምክንያቱ ደግሞ አስተሳሰባችን ከጠላት ተኮር ሥነ ልቡና ባለመላቀቁ ነው፡፡ ልክ ነው ግብጻውያን አሁንም በዴር ሡልጣን ገዳማችን ላይ ግፍ ይፈጽማሉ፡፡ አሁንም ችግር ይፈጥራሉ፤ አሁንም ገዳሙ እንዳይጠገን ይከላከላሉ፤ ህልውናችን ያበሳጫቸዋል፤ ብዛታችን ያንገበግባቸዋል፡፡ በግብጻውያን ምክንያት የተቀበልናቸው ብዙ መከራዎች አሉ፡፡ እንዳንሠራ የታገድናቸው ነገሮች አሉ፡፡ ግን የሁሉም ነገር መነሻና መድረሻ ግብጻውያን ናቸው ብለን መደምደም አንችልም፡፡ አንዳንዴም ‹‹እኛን የጨረሰን የራሳችን ጠማማ ነው›› እንዳሉት ዛፎች ለግብጻውያን ችግር ፈጣሪነት መነሻ እኛው ሆነን እንገኛለን፡፡
ታሪክ እንኳን እንደሚያስተምረን የዴር ሡልጣን ዋናው በር በግብጻውያን እጅ የቀረው ቁልፉ ለኢትዮጵያውያን እንዲሰጥ በተወሰነ ጊዜ በንጉሥ ምኒሊክ ተወካይና በገዳሙ ተወካይ መካከል ‹‹ቁልፉን መረከብ ያለብን እ ኔ ነኝ›› በሚል በተነሣው ውዝግብ ምክንያት ነበር፡፡ ዛሬ በየዓመቱ በስቅለት ቀን መብራት ይዘን እንለፍ አንለፍ የሚለው ውዝግብ የተፈጠረበት አንዱ ምንያት የኛው ጳጳስ በሰጡት ፈቃድ ነው፤ በገዳሙ በር አጠገብ ያሉት የብረት ቅስቶች የተገነቡት የኛው ጳጳስ በሰጧቸው ፈቃድ ነው፡፡
ግብጻውያን ጠንካራ ብሔራዊ ኮሚቴ አቋቁመን የዴር ሡልጣንን ነገር ዓለም ዐቀፋዊ አጀንዳ እንዳናደርገው አላገዱንም፤ ግብጻውያን በየዓመቱ የሚመጡ ምእመናንን በሚገባ እንዳናስገነዝብ አላገዱንም፤ ግብጻውያን እያንዳንዱ አጓጓዥ እንደ አይጥና ድመት እንዲተያይ አላደረጉም፤ ግብጻውያን በኢትዮጵያና በግብጽ ቤተ ክህነት በኩል ድርድር እንዳይጀመር አላደረጉም፤ ግብጻውያን ለሀገሩ የሚመጥኑ አባቶችን እንዳንመድብ አልያዙንም፤ ግብጻውያን ስለ ገዳማችን ተገቢውን መረጃ እንዳናስተላልፍ እጃችንን አልቆለፉንም፤ ግብጻውያን ምእመናን ተሳላሚዎችን አስተባብረን ሥራ እንዳናሠራ አላሳገዱንም፡፡
ጠላት ሁለት ጊዜ ይጎዳሃል፡፡ የመጀመሪያው በጠላትነቱ የሚሠነዝረው ጥቃት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በእርሱ እያመካኘህ ችግርህን ወደ ውስጥ እንዳታይ ማድረጉ ነው፡፡ ከሁለቱም የሚከፋው ሁለተኛው ነው ይባላል፡፡ የሁሉም ነገር ምክንያትና ሰበብ ጠላትህ ይሆናል፡፡ ሰዎችም በቀላሉ ይቀበሉሃል፡፡ አንተም ለማስረዳት ብዙ አትቸገርም፡፡ ለራስህም የችግርህ ሁሉ ምንጭ አድርገህ ትቀበለውና ሌሎች ነገሮችን አትመለከትም፡፡ አመለካከትህ ጠላት ተኮር ይሆናል፡፡

በኢየሩሳሌም ገዳሞቻችንም የሚታየው ይኼው ነው፡፡ ለማንኛውም ነገር ምክንያቶቹ ግብጻውያን ናቸው፡፡ ስለ ራሳችን ድክመት የሚያወራ የለም፡፡ ራሱን የሚወቅስም አልተገኘም፡፡ ብዙ ችግሮቻችን ግን ግብጻውያን ባይኖሩም የሚኖሩ ናቸው፡፡ ከጠባያችን፣ ከአሠራራችንና ከአካሄዳችን የሚመነጩ ናቸው፡፡ የግብጻውያኑ ችግርም መፍትሔ ያላገኘው እኛ ስለያዝነው ይመስለኛል፡፡ ነገሩን ጠበቅ አድርገን በመያዝ ብርቱ ሃይማኖታዊ፣ ዲፕሎማሲያዊና ፖለቲካዊ ጫና ለማሳረፍ የምናደርገው ጥረት አለመኖሩ፡፡ የዴር ሡልጣን ነገር ትዝ የሚለን ለትንሣኤ በዓል ጊዜ መሆኑ፤ ከዚያ በቀር ይህን ጉዳይ ሥራዬ ብሎ የያዘ አንድም ቤተ ክህነታዊ አካል አለመኖሩ፡፡ ግብጾችኮ ጉዳዩን በፓርላማ ደረጃ በብሔራዊ ኮሚቴ ነው የሚከታተሉት፡፡ እኛኮ እንኳን ፓርላማ ቤተ ክህነት የሚያውቀው ኮሚቴ የለም፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም ቢሆን ከኢየሩሳሌም ገዳማት በሚቀርብ ጥያቄ ይወያያል እንጂ የኢየሩሳሌም ገዳማትን ጉዳይ በዝርዝር አጥንቶ፣ የድርጊት መርሐ ግብር ቀርጾ፣ አካል አቋቁሞ፣ ከሚመለከታቸው ጋር ኅብረት መሥርቶ ዘላቂና ተከታታይነት ያለው ሥራ አይሠራም፡፡ አብዛኛው የኢየሩሳሌም ገዳማትን የሚመለከተው አጀንዳም ‹‹አቡነ እገሌ ይነሡ አይነሡ›› በሚለው ላይ የሚያተኩር ነው፡፡
በፓትርያርኮች ደረጃ በግብጽ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን መካከል ውይይት ሲደረግም የኢየሩሳሌም ገዳማችን ጉዳይ አጀንዳ ሆኖ የተነሣበት ጊዜ የለም ማለት ይቻላል፡፡ ቢያንስ ውይይት ለመጀመር፣ ችግሩን ለመፍታትና አንዳች የስምምነት ደረጃ ላይ በየእርከኑ ለመድረስ የሚያስችል መግባቢያ እንኳን የለም፡፡ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በቅርቡ ወደ ግብጽ ይሄዳሉ፡፡ እስከ አሁን ባለኝ መረጃ ዴር ሡልጣን የአጀንዳቸው አካል የሆነ አይመስለኝም፡፡ ለግብጻውያን ግን ዴር ሡልጣን ከዓባይ ቀጥሎ ከኢትዮጵያን ጋር ላላቸው የዲፕሎማሲ ግንኙነት አንዱ አጀንዳቸው ነው፡፡
ይህንን በዚህ እንተወውና ለመሆኑ ወደ ኢየሩሳሌም ገዳማት የምንመድባቸው አባቶች መመዘኛቸው ምንድን ነው? የሃይማኖት ትምህርት፣ የእምነት ጽናት፣ ለጸሎትና ለአገልግሎት ያላቸው ፍላጎት፣ ለመማር ያላቸው ትጋት፣ ከአካባቢው ጋር ተዛምደው ለመኖር ያላቸው ዝግጁነት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ አምባሳደር ለመሆን ያላቸው ችሎታ ይታያል? ከዐሥር ዓመታት በላይ ተቀምጠው ዐረብኛና ዕብራይስጥ የማይችሉ ከሆነ ኢየሩሳሌም መኖር ጥቅሙ ምንድን ነው? አገልግሎቱ ሲሆን ከሀገር ቤት ካልበለጠ ካልሆነም እንደ ሀገር ቤቱ ካልሆነ በኢየሩሳሌም ገዳማት መኖሩ በአሜሪካ ከመኖር ልዩነቱ ምንድን ነው? በኢየሩሳሌም ገዳማችን ደረጃውን የጠበቀ፣ አባቶችን ለዓለም አቀፋዊ አገልግሎት የሚያበቃ ትምህርት ቤት ከሌለን ኢየሩሳሌም መመደብ ከሥጋዊ ዕድል በዘለለ ጥቅሙ ምንድን ነው? የራሳችን የቅብዐ ቅዱስ ማዘጋጅ፣ የዕጣን መቀመሚያ፣ የንዋያተ ቅድሳት ማዘጋጃ፣ የመስቀል መሥሪያ፣ ከሌለን ኢየሩሳሌም መመደብ ጥቅሙ በዶላር ደመወዝ ማግኘት ነው ማለት ነው፡፡
የኢየሩሳሌም ገዳማችን ቤተ ክርስቲያናችን ከሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ጋር ያላትን ግንኙነት የሚያጠናክሩ፣ ከአካባቢው ባለ ሥልጣናት ጋር በሚገባ ተግባብተው የገዳማችንን መብት የሚያስከብሩ፣ በልዩ ልዩ ሞያ ሠልጥነው ለነገዋ ቤተ ክርስቲያን ተስፋ የሚሆኑ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን ለማወቅ የሚመጡትን ምሁራን በደረጃቸው የሚያናግሩ፣ በማንኛውም መድረክ ተገኝተው ቤተ ክርስቲያንን ሊወክሉ የሚችሉ፣ ልዩ ልዩ የገቢ ምንጭ ፈጥረው የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን የሚረዱ ተቋማትን የማያፈሩ ከሆነ መነኮሳቱ ‹‹አረዳ ጠባቂ›› ከመሆን ያለፈ ለቤተ ክርስቲያን በቁዔታቸው ምንድን ነው? መቼም ይህንን ሁሉ ያላደረግነው በግብጻውያን ምክንያት ነው አንልም፡፡

በዚህ በትንሣኤ ሰሞን ከዐሥር ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን ምእመናን በኢየሩሳሌም ተገኝተው ነበር፡፡ ነገር ግን እነርሱን በአንድ ጉባኤ ለማስተባበር፣ ስለ ገዳማቱ ሁኔታ በቂ ግንዛቤ ለመፍጠር፣ ፕሮጀክት ቀርጾ ያንን እንዲተገብሩ ለማድረግ፣ ምእመናኑን ለማስተማርና ለማነጽ፣ ጥረት ሲደረግ አላየሁም፡፡ ከዚያ ይልቅ የሀገር ቤቱ አሠራር አልለቀን ብሎ አንዳንድ ቁራጭ ጧፍ ለመሸጥ ነበር መከራ ስናይ የከረምነው፡፡ ውኃ አዙሮ ለመሸጥ ነበር ጥረት ሲደረግ የነበረው፡፡ ምእመናኑን በሚገባ አስረድቶ፣ ዘላቂ ነገር እንዲሠሩ አወያይቶ፣ ለልጅ ልጅ የሚተርፍ ነገር ከመሥራት ይልቅ አንድ ሺ ጧፍ ሽጦ አንድ ሺ ዶላር ለማግኘት መድከሙ በዋናው አልጋ ላይ መተኛት ሲቻል በትራሱ ላይ እንደ መተኛት ነው፡፡
ተሳላሚ ምእመናኑም ራሳቸውን እንደ ቱሪስት ቆጥረው ተሳልሞ ለመጓዝ ከመትጋት ባለፈ የገዳሙን ሁኔታ ለማወቅ፣ ዘላቂና ችግር ፈች ሥራ ለመሥራት፣ አልከፈት ያለውን የቤተ ክህነት በር በሚገባ አንኳኩቶ ለማስከፈት አልቻልንም፡፡ አጓጓዦቹም ምእመናኑ ተገናኝተው፣ ተዋውቀውና ተወያይተው፣ በአንድ ኢትዮጵያዊ መንፈስ አንድ ሥራ እንዲሠሩ ጥረት ሲያደርጉ አይታዩም፡፡ እንዲያውም ተጓዦቻቸው ባለመተዋወቅና በመፈራራት የጎሪጥ እንዲተያዩ ያደርጓቸዋል፡፡
እነዚህን ለምሳሌነት የጠቀስኳቸው በግብጻውያን ብቻ እያመካኘን በመቀመጣችን ያልሠራነው ሥራ ምን ያህል ዋጋ እያስከፈለን መሆኑን ማየት እንድንችል ነው፡፡ ግብጻውያን ርስታችንን ከመንጠቃቸው በላይ በእነርሱ እያመካኘን የኛን ሥራም እንዳንሠራ አድርገውናል፡፡ አሁን ለዴር ሡልጣን መልካም ዘመን ነው፡፡ ኢትዮጵያ በግብጽ ላይ አንገቷን ቀና አድርጋለች፣ የአካባቢው የፖለቲካ ምሕዳር እየተቀየረ ነው፡፡ ምእናንም በብዛት ወደ ኢየሩሳሌም እየመጡ ነው፡፡ ከመላው ዓለምም ተሳላሚዎች እየበዙ ነው፡፡ ይህንን እግዚአብሔር የሰጠንን ዕድል ካልተጠቀምን እንነጠቃለን፡፡ ስለዚህ በአዲስ አስተሳሰብ፣ በአዲስ መንፈስና በአዲስ መንገድ መነሣት አለብን፡፡
እንዴት? በቀጣይ ዐሥር ነገሮችን እጠቁማሁ፡፡
ዴር ሡልጣን፣ ኢየሩሳሌም

Viewing all articles
Browse latest Browse all 13695

Trending Articles



<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>