Quantcast
Channel: Amharic News & Opinion
Viewing all articles
Browse latest Browse all 13695

ዴር ሡልጣን፡- ዐሥር ነገሮች (ክፍል አምስትና የመጨረሻው ክፍል)

$
0
0
ባለፈው ጊዜ በተከታታይ የዴር ሡልጣንና ከዚያም ጋር የሚያያዙ ጉዳዮችን ስናነሣ ነበር፡፡ ምን መደረግ አለበት በሚለውም ዙሪያ ስድስት ነጥቦችን አንሥተናል ዛሬ የመጨረሻውን ክፍል እነሆ፡፡
7. ዲያስጶራውን ማንቀሳቀስ
ወደ ኢየሩሳሌም ቅዱሳት መካናትን በመሳለም ረገድ ዲያስጶራ ኢትዮጵያውያን ብዛታቸው እየጨመረ ነው፡፡ በውጭ የሚገኙት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትም ቁጥር ከዓመት ዓመት እጨመረ ይገኛል፡፡ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን እንዲሆን ለኢትዮጵያ ታሪክ፣ ቅርስና ዝና ተቆርቋሪ የሆኑትን ሌሎች ወገኖች በማስተባበር ዲያስጶራው የዴር ሡልጣንን  ይዞታ በማስጠበቅ፣ ዲፕሎማሲያዊ ሥራ በመሥራትና የሕግ ድጋፍ በማድረግ ተግባራት ላይ እንዲንቀሳቀስ ማድረግ ይገባል፡፡
አንዳንድ በአሜሪካን ሀገር የሚገኙና ከሲኖዶሱ የተለዩ ወገኖች ክፍፍሉን ወደ ኢየሩሳሌም ለማዝመትና በቅድስቲቱ ሀገር እርስ በርሳቸው የማይስማሙ ሁለት ማኅበረሰቦችን ለመፍጠር፣ ጥንታዊው ቦታም ተረስቶ እንዲቀር የሚያደርጉትን ጥረት በመግታት በኢየሩሳሌም ቅዱሳት መካናት ጉዳይ የተባበረ እና የማይከፋፈል የኢትዮጵያውያን ድምጽ እንዲኖር ማድረግ ያሻል፡፡
በእሥራኤል የሚገኙ የኢትዮጵያ ቅዱሳት መካናትን በተመለከተ ዓለም ዐቀፋዊ ሲምፖዝየምና የውይይት መድረክ በማዘጋጀት፣ ዐውደ ርእዮችን በማቅረብ፣ ግብጾች በገዳሙ ላይ የሚያሳድሩትን ተጽዕኖ በዓለም ዐቀፍ መድረኮች በመገዳደር፣ ጉዳዩ የዓለም ዐቀፍ ሚዲያዎችን ትኩረት እንዲያገኝ በማድረግ፣ የዴር ሡልጣን መነኮሳት እየኖሩበት ያለው የአኗኗር ሁኔታ ከዓለም ዐቀፍ የሰዎች የመኖርና የመኖሪያ ቦታ መብት አንጻር ያለበትን ደረጃ በማሳየት፣ የሰብአዊ መብት ተከራካሪዎች ለመነኮሳቱ የመኖርና ለመኖር የሚያስፈልጓቸውን ነገሮች የማግኘት መብት እንዲሟገቱ በመወትወት ዲያስጶራው የማይናቅ አስተዋጽዖ ሊያደርግ ይችላል፡፡

8. ቤተ እሥራኤላውያንን ማንቀሳቀስ
ኢትዮጵያ ውስጥ ለሺ ዓመታት የኖሩ ቤተ እሥራኤላውያን ዛሬ በእሥራኤል ይገኛሉ፡፡ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ፍቅርና ክብር ያላቸው፣ ጉዳያችንንም ጉዳያቸው የሚያደርጉ ቤተ እሥራኤላውያንም አሉ፡፡ የሩሲያ ቤተ ክርስቲያን ከሩሲያ በመጡ ቤተ እሥራኤላውያን የምታገኘውን ድጋፍ ምሳሌ ያደረገ ድጋፍ እንዲያደርጉ ቤተ እሥራኤላውያንን ማስተባበር ይቻላል፡፡
በእሥራኤል ፓርላማ ጉዳዩ እንዲታይ፣ የግብጻውያን ጫና እንዲቀንስ፣ የኢትዮጵያውያን መነኮሳት የመኖር መብት እንዲከበር፣ የቦታው የባለቤትነት ክርክር እንዳለ ሆኖ ነገር ግን በእሥራኤል የኑሮ ደረጃ ለአንድ ሰው የሚያስፈልጉት መሠረታዊ ፍላጎቶች ለዴር ሡልጣን መነኮሳት እንዲሟሉ፣ በዴር ሡልጣን በሚገኙት የሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት ማኅበረሰቦች መካከል መለስተኛ ውይይቶች እንዲጀመሩ በማድረግ ረገድ ቤተ እሥራኤላውያን የማይተካ ሚና ሊጫወቱ ይችላሉ፡፡
9. ጠንካራ የገዳም ሕግ ማውጣት
በእሥራኤል የሚገኙት የኢትዮጵያ ገዳማትና ገዳማውያንን የሚመለከት ጠንካራ ገዳማዊ ሕግ ያስፈልጋል፡፡ ትምህርትና፣ አገልግሎትን፣ ሥራን፣ ጸሎትን፣ የንብረት አስተዳደርን፣ ከገዳም መውጣትንና መግባትን፣ ሀብትን፣ የዲሲፕሊን ሕጎችንና ሌሎች ጉዳዮችን የተመለከቱ ሕጎች ያስፈልጋሉ፡፡ ለመሆኑ ቅዳሴ በፍላጎት ነው የሚከናወነው? ሰው የሚጠፋበት ጊዜ የለም? የሌሊቱ አገልግሎትስ ሰላም ነው? አንድ መነኮስ ጠዋት ኪዳን ካደረሰ ወይም የአገልግሎት ተረኛ ካልሆነ ምን ሲሠራ ነው መዋል ያለበት? ለአስጎብኝነት ተግባርስ የሚመድበው ማነው? ወደ ሌሎች አገሮች የሚደረገው ጉዞስ እንዴት ነው መፈቀድ ያለበት? አንድ መነኮስ ንግድ ማካሄድ ይችላል? ለመሆኑ ሁሉን መነኮሳት የሚመለከት የጸሎት መርሐ ግብር አለ? ወይስ ለጸሎት የሄዱ መነኮሳት ሰሞነኛ መሆን አለባቸው? ገዳሞቻችን ጠንካራ የዲስፕሊን ሕግ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ መነኮሳትን በተመለከተ የኢየሩሳሌም ተሳላሚ አውሮፓውያን የጻፏቸው መዛግብት ሁሉ ለጸሎት፣ ለትምህርትና ለፍጹማዊ ምናኔ የሚሰጡትን ቦታ በአድናቆት የሚያነሡ ናቸው፡፡ በ18ኛው መክዘ በሊባስ የነበረ አንቶንዮ የተባለ ፍራንቺስካን ስለ ኢየሩሳሌም መነኮሳት በጻፈው አንድ የጉዞ ማስተዋሻ ላይ ‹‹ወደ ጎልጎታ በሚወስደው መንገድ ላይ በአነስተኛ ቤተ መቅደሶች የሚገለገሉ ኢትዮጵያውያን ይገኛሉ፡፡ እነዚህ መነኮሳት ወደ ሊባኖስ በየዓመቱ ይዘልቃሉ፡፡ እነርሱ ሲመጡ ለመባረክ የኛ ምእመናን ሳይቀሩ ትተውን ይሄዳሉ፡፡ ልብሳቸው አዳፋ ነው፡፡ አንዳንዶቹም ቆዳ ይለብሳሉ፡፡ ሕዝቡ ልብሳቸውን ቀድዶ ይወስደዋል፡፡ ለእነርሱም የሚበቃቸውን እህል ይሰጧቸዋል፡፡ የሚመጡበት ወቅት እዚህ በጉጉት ነው የሚጠበቀው›› ይላል፡፡ ይኼ ነገር ዛሬ እንጥፍጣፊውስ አለ?
10. የተቀናጅ ስትራቴጂያዊ ዕቅድ
ዴር ሡልጣንንና ሌሎች በቅድስት ሀገር የሚገኙ ቦታዎቻችንን በተመለከተ የሚነሡ ነገሮች ሁሉ ድንገቴዎች ናቸው፡፡ አሁን ባሳለፍነው የትንሣኤ በዓል እንኳን ስምንት መቶ ሺ ዶላር ስለሚያወጣ ቦታ ግዥ ሲነገር ነበር፡፡ ከዚህ በፊትም ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ የተጠመቀበትን ቦታ ስለመግዛት ይነሣ ነበር፡፡ ጃንደረባው የተጠመቀበት ቦታ ግዥ የት እንደደረሰ ሳይታወቅ አሁን ደግሞ ሌላ ሃሳብ መጣ፡፡ የዚህኛው ግዥም ቢሆን ዝርዝር ፕሮጀክቱ አልተገለጠም፡፡ እንዴው ብቻ ገንዘብ አዋጡ ነው የተባለው፡፡
የኢየሩሳሌም ቅዱሳት መካናትን በተመለከተ ሊኖረን የሚገባው አሠራር የተቀናጀና የታሰበበት ስትራቴጂያዊ ዕቅድን የተከተለ መሆን አለበት፡፡ አባቶች በተቀያየሩ ቁጥር የማይቀየር፣ በሚገባ ታስቦበት ቢያንስ ለዐሥር ዓመት እንዲያገለግል ሆኖ የተዘጋጀ፣ የሁሉንም ተሳትፎ ያካተተ መሆን ይገባዋል፡፡ አንዱ ተነሥቶ ይህንን እንገንባ፣ ሌላው ተነሥቶ ያኛውን እንግዛ፣ ሌላው ተነሥቶ ይህን እናሠራ ማለት የለበትም፡፡ የገዳሙ የወደፊት ዕድገት፣ ያሉበት ችግሮች፣ ችግሮቹን እንዴት በቅደም ተከተል መፍታት እንደሚቻል፣ ለዚህ የሚያስፈልገው ወጭ፣ ወጭው ከየት እንደሚሸፈን፣ የሚሠራው ነገር የአስተዳደሩ ጉዳይ፣ በሚገባ ሊመለሱ ይገባቸዋል፡፡
በጣም የሚገርመው ነገር ኢየሩሳሌም ላይ ሕዝቡን አስተባብሮ ዘመን የሚሻገር ሥራ መሥራት ሲቻል ምእመናን ሁልጊዜ የሚነገራቸው በአልዓዛር ለሚገኙ አረጋውያን ጋቢ እንዲያመጡ ነው፡፡ ለምን ዘላቂ በሆነ መንገድ ችግራቸውን አንፈታውም? ዛሬ ወጣት መስለው የሚታዩት መነኮሳትስ ነገ እዚያ አይደለም እንዴ የሚጦሩት? ያ ሁሉ ጋቢ እዚያ ምን እንደሚሠራ መድኃኔዓለም ይወቀው፡፡
በአሁኑ ጊዜ አስጎብኝዎቹ በዝተዋል፡፡ ሁኔታውን ስናየው የማስጎብኘቱ ሥራ ከመጀመሪያው ትውልድ ወደ ሁለተኛው ትውልድ እየተሸጋገረ ነው፡፡ ከዛሬ አርባና ሃምሳ ዓመታት በፊት ማስጎብኘቱን የጀመሩት አካላት በአዳዲስ ትኩስ ኃይሎች እየተተኩ ነው፡፡ ይህንን ዕድል በተቀናጀ ስትራቴጂ መምራት ያስፈልጋል፡፡ እያንዳንዱ አስጎብኝ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ዐውቆ፣ ለዚያም ተዘጋጅቶ እንዲሠራ ያደርገዋል፡፡ ለተሳላሚነት የሚመጣው ሕዝብም በየዓመቱ በተሠራው ላይ እየተወያየ በቀረው ላይ እየጨመረና የራሱን ኃላፊነት እየወሰደ እንዲያበረክት ያደርገዋል፡፡ አንድ ትውልድ ሲያልፍ አሻራውን አስቀምጦ እንዲያልፍም ያደርጋል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ወደ ኢየሩሳሌም በአዲስ መንገድ ጉዞ የተጀመረበትን ሃምሳኛ ዓመት እያከበርን ባለንበት ዘመን ላይ ሆነን የሠራነውን ሥራ ብንገመግመው ሕዝብ ከማጓጓዝ የዘለለ ውጤት አናገኝበትም፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ገዳሞቻችን የዕጣን መቀመሚያ፣ የሻማ መሥሪያ፣ የጠበል ማሸጊያ፣ የቅብዐ ቅዱስ ማዘጋጃ፣ የቅዱሳት ሥዕላት ማተሚያ፣ የቅዱሳት መጻሕፍት ማዘጋጃ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ያ ሁሉ ተሳላሚ ወደ ገዳሞቻችን ሲሄድ የሚገዛው ቅብዐ ቅዱስ፣ ዕጣንና ጠበል ከሌሎች አብያተ ክርስቲያናት በርካሽ ተገዝቶ የሚከፋፈል እንጂ በኛው ቤተ ክርስቲያን የተዘጋጀ አይደለም፡፡ ይህ አሳዛኝም አሳፋሪም ነው፡፡ ሁሉም ነገር እያለ፣ የሰው ኃይሉም ተከማችቶ፣ ለመሥሪያ የሚሆን ቦታ ሳይጠፋ የሰው ንብረት ማከፋፈያ እንደመሆን ያለ አሳዛኝ ነገር አልነበረም፡፡
ሲሆን የኢየሩሳሌም ገዳማት ለሀገር ውስጥ አብያተ ክርስቲያናት መትረፍ ነበረባቸው(‹ጳጳሱ ቄስ ናቸው ወይ ቢሉ ተርፏቸው ለሰው ይናኛሉ› እንደተባለው) ካልሆነ ደግሞ ቢያንስ ለራሳቸውና ለተሳላሚዎች የሚተርፍ ነገር መኖር ነበረበት፡፡ በጣም የሚገርመው ነገር በገዳሞቻችን የገዳማቱን ታሪክ እንኳን የሚገልጥ በራሪ ወረቀት አይገኝም፡፡ ፖስት ካርድማ በሥዕለትም አታገኙ፡፡ በሌሎቹ አብያተ ክርስቲያናት ያያችሁ እንደሆነ እስከ 11 በሚደርሱ ቋንቋዎች የተዘጋጁ ገዳማቱን የሚገልጡ ወረቀቶች ታገኛላችሁ፡፡ አንድ ሸክል(የእሥራኤል ገንዘብ) አስቀምጡና ውሰዱ ይሏችኋል፡፡ ሞያ ከጎረቤት መማር ለምን እንዳቃተን እንጃ፡፡
ባለፈው በክፍል አንድ ላይ ይህንን ሃሳብ በመጠኑ ተነሥቶ ነበር፡፡ የገዳሙ መነኮሳት በምሳ ሰዓት ተሰብስበው በወሰኑት መሠረት በሰጡት መልስ ግን የኛ ሥራ ጸሎት እንጂ ተግባረ ዕድ አይደለም ብለዋል፡፡ ለዚህ እኔ መልስ ከምሰጣቸው የመነኮሳት አባቶች ከሚባሉት አንዱ አባ ስልዋኖስ ያደረገውን ልንገራቸው፡፡ አንድ ወንድም አባ ስልዋኖስን ለማየት ወደ ደብረ ሲና ወጣ፡፡ በዚያ የሚገኙ ወንድሞችም ተግተው ሲሠሩ ተመለከተና ለአባ ስልዋኖስ ‹‹ለሚጠፋ ምግብ አትድከሙ፣ ማርያምስ የማይቀሟትን ዕድል መረጠች ተብሏል›› አለው፡፡ አባ ስልዋኖስም ዘካርያስ የተባለ ረድኡን ጠርቶ ‹‹ይህንን ወንድም መጽሐፍ ስጠውና በበኣት ውስጥ አስቀምጠው›› አለና አዘዘው፡፡
ያ እንግዳ ወንድምም ዘጠኝ ሰዓት ሲሆን ምናልባት አንድ ሰው ለማዕድ ይጠራኝ ይሆናል ብሎ ጠበቀ፡፡ የጠራው የለም፡፡ የሚጠራው ሲያጣ ወደ አባ ስልዋኖስ ሄደና ‹‹ዛሬ ወንድሞች ምግብ አይመገቡም እንዴ›› ሲል ጠየቀው፡፡ አባ ስልዋኖስም ተመግበው መጨረሻቸውን ነገረው፡፡ ያ ወንድምም ‹‹ታድያ እኔን ለምን አልጠሩኝም›› አለው፡፡ አባ ስልዋኖስም ‹‹አንተ መንፈሳዊ ስለሆንክ ይህንን መሰሉን ምግባር አትፈልገውም ብለን ነው፤ እኛ ግን ሥጋውያን ስለሆንን እንመገባለን፡፡ የምንሠራውም በዚህ ምክንያት ነው፡፡ አንተ ግን የማይቀሙህን ዕድል መርጠሃልና ቀኑን ሙሉ መጽሐፍ ብቻ ታነባለህ፡፡ አላፊ ጠፊ ምግብ አያስፈልግህም›› አለው፡፡ ይህንን ሲሰማ ያ ወንድም በግንባሩ ተደፍቶ ‹‹ይቅር በለኝ›› አለው፡፡ አባ ስልዋኖስም ‹‹ለማርያም ማርታ ታስፈልጋታለች፤ ማርያም የተመሰገነችው በማርታ ምክንያት ነውና ለማርታ ምስጋና ይግባት›› አለው፡፡
ከትናንት ብንዘገይ ከነገ መቅደም አለብንና ስንፍናውን አስወግደን ዛሬ ብንነሣ እንደርሳለን፡፡ በገዳማቱ ውስጥ ነገሩ እንደ እግር እሳት የሚለበልባቸው፣ ለተልዕኮ ለመፋጠን የማይሰለቹ፣ ገዳማቸውን ከሌሎች እኩል ሆኖ ለማየት የሚተጉ ብርቱ መነኮሳት መኖራቸውን ማንም ያየዋል፡፡ ምንም ጥቂት ቢሆኑ፡፡ እነርሱን አንቀሳቃሽ ሞተር አድርጎ ሥራውን መሥራት ነው፡፡ ኢየሩሳሌም ላይ እንደዚህ የተቀናጀና መሥመር ያለው ሃይማኖታዊ ሥራ መሥራት የሀገር ቤቶቹን ገዳማትና አድባራት መንፈስም የሚቀሰቅስ ይሆናል፡፡ እነዚህ አባቶች ነገ በቤተ ክርስቲያኒቱ ታላላቅ ኃላፊነት ላይ ሲመደቡም በኢየሩሳሌም የለመዱትን እዚህ ሀገር ቤትም እንዲተገብሩት ያደርጋቸዋል፡፡
ማጠቃለያ
የኢየሩሳሌም ገዳማት ጉዳይ በማንም እጅ ላይ አይደለም፡፡ በራሳችን እጅ ላይ ነው፡፡ የደከምነውም እኛ ነን የምንበረታውም እኛው ነን፡፡ ግብጾች በደንባራ በቅሎ ላይ ቃጭል ይጨምራሉ እንጂ ደንባራዋን በቅሎ አያመጧትም፡፡ በብኾር ላይ ቆረቆር ያመጣሉ እንጂ ብኾሩ የኛው ነው፡፡ እኛን ለመጥረቢያ እጀታ ሆኖ የፈጀን የራሳችን ጠማማ ነው እንዳሉት ዛፎች ችግሩ እኛው ነን፡፡ ስለዚህም ቁጭ ብሎ መነጋገር፣ መፍትሔ መፈለግና ዕቅድ ማውጣት ያስፈልጋል፡፡ ዓለም በፈጣን ሁኔታ እየተቀያየረ ነው፤ ሁል ጊዜ እየየ አያዋጣም፡፡ የሚያዋጣው መንፈሳዊ ሆኖ፣ ሠርቶ፣ ተግቶና ዓለምን አሸንፎ መለወጥ ነው፡፡ ለጊዜው እኔም በዚሁ ላብቃ፡፡ ጽሑፉ ከተጀመረ በኋላ የገዳሙ መነኮሳትና ሌሎች ምእመናን የላኩልኝን ሰነድና መረጃ አጠናክሬ ደግሞ ሌላ ጊዜ እመለሳለሁ፡፡ ቸር ይቆየን፡፡

Viewing all articles
Browse latest Browse all 13695

Trending Articles



<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>