Quantcast
Channel: Amharic News & Opinion
Viewing all articles
Browse latest Browse all 13695

እውን ፍቅር ያሸንፋል? ሽመልስ ከተማ

$
0
0

የቴዲ-አፍሮ እና የፕ/ር ኤፍሬም ይስሃቅ የፍቅር ያሸንፋል ጽንሰ-ሀሳቦች ( concepts) ብዙ አይገቡኝም፤ ፍቅር ነክቶኝ ስለማያውቅ ወይም የፍቅር የስበት ሃይል ሳይገባኝ ቀርቶ አይደለም፣ በቤተሰብ ደረጃ ቢሆን ይገባኛል፤ ከቤተሰብ አልፎ ግን ፍቅር እንዴት አድርጎ የአንድን አገር ውስብስብ ችግሮች ሊፈታ እንደሚችል ባስብ ባስብ መልሱ አልታይህ ብሎኛል። ፕ/ር ኤፍሬም ይስሃቅ በአዲስ አድማስ ላይ “የኢትዮጵያ ( ሰላም) መሠረቱ ህዝቡ ነው፡፡ ህዝቡ ባህል አለው፤ መንፈሳዊ ህዝብ ነው፤ ሰው የሚያከብር ነው፡፡ ከመካከላችን ግን አሉ፤ ሃይለኞች፡፡ በተለይ የማኪያቬሊን መጽሐፍ ያነበቡ፣ የማርክሲዝም ትምህርት ተምረው አንጐላቸው ትንሽ የዞረ ጥቂቶች አሉ ” ይላሉ። ፕሮፌሰሩ “ጥቂቶች” የሚሉዋቸው የእርሳቸውን “የፍቅር ፖለቲካ” አስተሳሰብ የማይቀበሉትን ነው፤ እኔም ከእነዚህ ጥቂት ከዞረባቸው ሰዎች መካከል ልመደብ እችላለሁ፣ አካሄዳቸው አይገባኝምና ። ችግሩ ግን እኔ የማኪያቬሌ ወይም የማርክስ ተከታይ አለመሆኔ ነው፣ ቃሊቲ እያለሁ የማርክስን “ዳስ ካፒታል” ለማንበብ ጀምሬ ሳልጨርሰው ወጣሁ፣ የማኪያቬሌን The Prince እና Discouses አይቻቸዋለሁ። ሁለቱም ፈላስፎች የእነ ፕ/ር ኤፍሬምን የ” ፍቅር ” ዜማ እንዳልቀበል ተጽእኖ አላሳደሩብኝም። ፍቅር ለዚህ አለም የህይወት ጣጣ መፍትሄ አለመሆኑን ለመከራከር እነዚህን መጽሀፎች ማንበብ አይጠበቅብንም ። ፍቅር ለወዲያኛው ዓለም ሊሰራ ይችላል፣ ለዚህኛውም ዓለም (ለምድራዊው) ግን አይሰራም ። ( በነገራችን ላይ የማኪያቬሌ ስም ብዙ ጊዜ አሉታዊ ከሆኑ ጉዳዮች ጋር ተያይዞ ሲቀርብ ይገርመኛል፤ የማኪያቬሌን The Prince ያነበበ ሰው ማኪያቬሌን የአምባገነኖች መካሪ አድርጎ ቢወስደው አይገርምም፣ ይሁን እንጅ Discourses ን ያነበበ ሰው ማኪያቬሌ ስልጣንን እንዴት መቆጣጠር እንደሚቻል ያመላከተ ፣ ለዛሬው የዲሞክራሲ መገለጫ ለሆነው check and balance ጽንሰ ሀሳብ መነሻ የሆነ ሰው መሆኑን ያደንቃል ። )

ወደ ዋናው ነጥባችን እንመለስ፣ አዎ! የፍቅር ያሸንፋል ጽንሰ ሀሳብ የአገራችንን ሁለንተናዊ ችግር አይፈታም!
አንደኛ! በአገራችን በስርዓቶች አማካኝነት ብዙ በደሎች ተፈጽመዋል፣ የሩቁን ትተን፣ ከአስር አመታት በሁዋላ የተፈጸሙትን እንኳ ብናይ በምርጫ 97 200 ሰዎች ተገድለዋል፤ ከዛ በሁዋላ በኦሮምያ፣ ኦጋዴን፣ አማራ፣ አፋር፣ ቤንሻንጉል ወዘተ ቁጥሩ የማይታወቅ ህዝብ ተገድሏል፣ ታስሯል፣ ተሰቃይቷል። በእነዚህ ችግሮች ላይ ሳንነጋገር፣ አጥፊዎች ጥፋታቸውን አምነው ሳይቀጡ ወይም ይቅርታ ሳይጠይቁ ፣ ፍቅር ያሸንፋል በማለት ብቻ ችግራችን አይፈታም፣ በደል የደረሰባቸው ሁሉ ፍትህ ማግኘት አለባቸው። ፍትህም የሚገኘው አንድም አጥፊዎች በነጻ ፍርድ ቤት ጉዳያቸው ታይቶ ተመጣጣኝ ህጋዊ ቅጣት ሲሰጣቸው ( retributive justice) ሌላም አጥፊዎቹ ጥፋታቸውን አምነው በመጸጸት በደል የደረሰባቸውን ሰዎች ይቅርታ ሲጠይቁና ችግሩ ዳግም እንዳይፈጠር መስራት ሲችሉ ነው ( restorative justice) ። ተበዳይም በዳይም በአንድነት ተቻችለው እንዲኖሩ፣ ቢፋቀሩ ባይፋቀሩ የራሳቸው ጉዳይ ነው፣ ለሁለቱም የሚሆን ስርዓት እስከሰፈነ ድረስ በቂ ነው፤ ተኩላዎችንም በጎችንም እንደጠባያቸው አድርጎ የሚያስተዳደርው ስርዓት ደግሞ ዲሞክራሲ ነው፤ ዲሞክራሲ ፍጹም አይደለም፣ ነገር ግን መፋቀር የማይችሉትን ሰዎች ተከባብረው እንዲኖሩ ያደርጋል፤ የሚፋቀሩትንም ሆነ የማይፋቀሩትን ሰዎች በአንድ ላይ ለማኖር ከዲሞክራሲ ውጭ ለሰው ልጆች የተሰጠው ሌላ የተሻለ ስርአት የለም። እናም ቴዲ በመረዋ ድምጹ እንዲሁም ፕ/ር ኤፍሬም በውብ ብእራቸው ስለፍቅር ከሚሰብኩ ስለዲሞክራሲ ምስረታ ቢሰብኩ የችግራችንን ቁልፍ አገኙት እላለሁ።

ቴዲ አፍሮ ፍቅር ካለ ቂምና ቁርሿችን ሁሉ ይፈታል ይለናል፣ እንዲህ ያብራራዋል፦ ” ትልቁ ነጥብ፣ ካለፍንበት ታሪክ ተነስተን ለሚቀጥለው ጊዜ ምን እናድርግ የሚለው ነው፡፡ ያዘንበትን ነገር በይቅርታ ሰርዘን፣ የወደድነውን ነገር ደግሞ አሳድገን ለመጓዝ፣ ትልቁ መድሃኒት ፍቅር ነው፡፡ ይቅር ተባብሎ የቀድሞ ስህተቶችን ለማስተካከልና በህብረት ተጠራርቶ የቀድሞ ትክክለኛ ነገሮችን ለማሳደግ፣ ፍቅር ያስፈልጋል፣ የዘመናችን ፈተናዎች ሳያንሱ፣ የቅርብ ጊዜ የቂም ታሪክንም እየተሸከመን፣ ከዚያም አልፎ የሩቅ ጊዜ የቅሬታ ታሪኩንም እየቆሰቆስን ቂምን የምናወርስ ከሆነ፣ ለማናችንም ሕይወት የማይጠቅም፣ የልጆቻችንንም ተስፋ የሚያጨልም አደጋ እየፈጠርን እናልፋለን፡፡ ቂምን መሻር፣ ቁስልን መፈወስ፤ ከዚያም አልፎ ለሁላችንም የሚበጅና የተስፋ ብርሃንን የሚያደምቅ ነገር መስራት የምንችለው በፍቅር ነው”። የምር ይሄ ታምረኛ ፍቅር ለእኔ አልገባኝም፣ እንዴት እንደሚገኝም አላውቅም፣ እንዴያውም ለእኔ ፍቅር ይመጣል ከተባለም፣ ይቅር ከተባባልን በሁዋላ እንጅ፣ ይቅር ሳንባባል እንዴት ሊመጣ እንደሚችል አይገባኝም፤ ከፈረሱ ጋሪው ቀድሞብኛል፤ ቴዲ እስከ እነ ችግራችን አፍቃሪ መሆን የሚያስችለን መድሃኒቱ ካለው ቢነግረን አይከፋም፣ አልያ ግን ንግግሩ ባዶ ጩኸት ይሆንብኛል። የቴዲ ምርጥ ንግግር የመጨረሻዋ ቃል ” ዲሞክራሲ” በሚል ቢተካ ኖሮ ቴዲን ከምርጥ ተናጋሪዎችና አሳቢዎች ዘንዳ እፈርጀው ነበር። እንግዲህ ይሄ የፍቅር ቋንቋ ለእኔ ስላልገባኝ የቴዲ አድናቂዎች አትፍረዱብኝ፣ ከቻላችሁ አስረዱኝና እኔም ” ወይ ፍቅር” እያልኩ አብሬው ልዘምር።

ሁለተኛ! “የፍቅር ያሸንፋል” ጽንሰ-ሀሳብ በምድራችን ላይ ተግባራዊ ይሆናል ብየ የማላስብበት ተጨማሪ ምክንያቶች አሉኝ። ሰዎች ሁሉ እኩል ናቸው የሚባለው በእግዚአብሄር ፊት እንጅ በሰዎች ፊት (በምድር ላይ) አይደለም፤ ሰዎች በሃብት፣ በእውቅት በክብር ወዘተ ይለያያሉ። አንዱ የብር ማንኪያ ይዞ ይወለዳል፣ ሌላው እንደተወለደ የእናቱ ጡት እንኳን ይደርቅበታል፤ አንዱ የመጽሀፉን ቃል አምኖ ጥሮ ግሮ ለመኖር ይታትርና ባዶ እጁን ይገባል፣ ሌላው ሞጭልፎ በሳምንት ውስጥ አየር ላይ ካልተኛሁ ይላል። ክርስትና “ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት እኩል ናቸው” ባይል ኖሮ ሃብታሞችና ድሆች እርስ በርስ የሚያደርጉት መገዳደል ይጨምር ነበር፣ አሁንም ይገዳደላሉ። በብሉይ ኪዳን “ደሃ ድህነቱን ይረሳ ዘንድ ወይን ይጠጣ” ይላል፣ የወይን መግዢያ የሌለው ድሃ ምን ጠጥቶ ድህነቱን እንደሚራሳ ግልጽ ባይሆንም፤ በአዲስ ኪዳን ደግሞ አባባሉ ተሻሽሎ “ሃብታም መንግስተ-ሰማያትን ከሚወርስ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢሾልክ ይቀለዋል” ይላል። ይሄ አባባል ለደሃው ትልቅ ተስፋ የሚሰጥ ነው- ለእነማርክስ የአመጽ ጥሪ ማርከሻ ወርቅ መልእክት። ደሃ፣ ደሃ በመሆኑ መንግስተ ሰማያትን እንደሚወርስ ከተነገረው ደሃ ሆኖ መኖር እንጅ ሌላ ምን ይፈልጋል? ቢሞትም በቀጥታ የሚገባበትን ያውቃል፤ ሀብት አካፍለኝ ብሎ በሃብታሙ ላይስ ለምን ያምጻል? እስልምና በዚህ ጉዳይ ምን እንደሚል አላውቅም።

አንዳንድ ጊዜ ሃይማኖቱን የማይከተሉ ድሆች በሃብታሞች ላይ ማመጻቸው አልቀረም። ለወደፊቱም ያምጻሉ፤ እንደዛ ማድረጋቸውም ስህተት ነው ብየ አላስብም፤ እንዴያውም ለእኔ ስህተቱ ደሃ እስከ ድህነቱ የሞተ ጊዜ ነው፤ ሰርቶ ካላለፈለት አምጾ መብላት አለበት። አለም እኮ ጎደሎ ነች። አንዱ ጠግቦ ሌላው ተርቦ የሚያድርባት፣ አንዱ ሌላውን አሸንፎ የሚኖርባት የፉክክር መድረክ ፤ ተሸናፊው ያዝናል፣ አሸናፊው ይደሰታል። የእነ ቴዲ ” የተፋቀሩ መልዕክት” ሀብታምና ደሃን፣ ተበዳይና በዳይን፣ አሸናፊና ተሸናፊን አፋቅሮ ሊያኖር አይችልም። በክሬን ቢሳቡ እንኳ አይፋቀሩም! ተቃራኒ ሃይሎች ሳይበላሉና ሳይጠፋፉ ፍላጎታቸውም እንደተጠበቀ ሊኖሩ የሚችሉት፣ እንዲፋቀሩ በመምከር ሳይሆን፣ ሁሉንም አስማምቶ የሚያኖር ስርአት ሲዘረጋ ነው፤ ያም ስርአት ከላይ የጠቀስኩት “ዲሞክራሲ” የሚባለው ነው። ምሁራን democracies rarely go to war ይላሉ። እውነታቸውን ነው፣ እስከዛሬ ዲሞክራሲ አገሮች ሲዋጉ አላየንም፣ ተፋቅረዋል ማለት ግን አይደለም፤ ዲሞክራሲ የፍቅር መገለጫ ሳይሆን እሰከነ ቂምና ቁርሾ ተቻችሎ የሚኖርበት ስርዓት ነው።

ሶስተኛ! በአይናችን እንዳየነውና ተጽፎም እንዳነበብነው ተረጋግተው የሚኖሩ አገሮች የመረጋጋት መሰረታቸው ፍቅር ሳይሆን ስርዓት ነው። እኔ የምኖርባትን ሆላንድ ( ኔዘርላንድንስን) ተመልከቱ ፤ መብት እንደልብ የሆነባት ፣ ግብረሰዶማዊው በአደባባይ የሚሳሳምባት፤ ሀሺሻሙም ፍላጎቱን የሚያረካባት ነጻ አገር ናት። እንደፈለግን ብንሆን ማን ከልካይ አለብን የሚሉ ሰዎች ያሉበትን ያክል “ቴሌቪዥን የሃጢያት ስር ነው” ብለው ቤታቸው ውስጥ ቴሌቪዥን የሌላቸው ሰዎችም አሉ፤ በሁለቱም አይነት ሰዎች ቤት ገብቼ ተስተናግጃለሁ። አንዱ ሌላውን አጥብቆ ይጠላል ፣ ነገር ግን ሁለቱም አይጠፋፉም፤ በአንድ ስርዓት ውስጥ ተቻችለው ይኖራሉ። ደቡብ ሆላንድ ካቶሊክ ነው፣ ሰሜኑ ደግሞ ፕሮቴስታንት ፣ ሁለቱም አይዋደዱም፣ ቂምና ቁርሾ አላቸው፣ ሁለቱም ግን ተከባብረው በአንድ ስርዓት ስር ይኖራሉ፤ አሜሪካም ጥቁሩና ነጩ ቂም አለው፣ በአውሮፓ ህብረትም ጀርመንና ፈርንሳይ ብርቱ ቂም አላቸው፤ እንዲህ እያሉ የአገሩን ታሪክ ሁሉ መዳሰስ ይቻላል፤ ዞሮ ዞሮ የምንደርስበት መደምደሚያ ግን ፣ “አገር ተረጋግቶ የሚመራው አንጻራዊ በሆነ መልኩ ለሁሉም በሚሆን ስርአት እንጅ በፍቅር አይደለም የሚለውን ነው።”

አራተኛ ምክንያት! ስለፍቅር የሚሰብኩት የሃይማኖት አባቶች ራሳቸው ሲጣሉ እናያለን ። ወደው እንዳይመስላችሁ ፣ እነሱም የሚኖሩት በዚህ በጎደሎው አለም ውስጥ ስለሆነ ነው። ቀሳውስቱም ሼኹም በዚህ አለም መኖር የሚችሉት አሸናፊ ሆነው ሲገኙ ብቻ መሆኑን ባይረዱትም ያውቁታል፤ ምድራዊ ስልጣን ይፈልጋሉ፣ አልያ ሌላው ቦታቸው ላይ ይወጣና የጨፈልቃቸዋል። ስለፍቅር ቢሰብኩም የሚኖሩት ውድድር ባለበት አለም ነው፤ ውድድር ባለበት አለም ደግሞ ” ፍቅር” ቦታ የለውም። የሃይማኖት አባቶቹ ተቻችሎ የሚያኖር ፍትሃዊ ስርዓት ከላገኙ እነሱም እንደሌላው መባላታቸው አይቀርም። ቴዲ አፍሮ ከሁለቱም የኢትዮጵያ አርቲስቶች ጋር ፍቅር ነው ቢባል የአለምን እውነታ መካድ ነው የሚሆነው። ፕ/ር ኤፍሬምም ከሁሉም ሽማግሌዎች ጋር ፍቅር ናቸው ቢባሉ መዋሸት ነው የሚሆነው። እነሱም ከሁሉም ጋር ፍቅር ነን አይሉም፤ ነገር ግን ቴዲ ከአርቲስቶች ጋር ባይፋቀር እንኳ፣ ተወዳድሮ እንዲኖር የሚያደርገው ፍትሃዊ ስርዓት ያስፈልገዋል።

አምስተኛ! ከፍቅር ያሸንፋል ጀርባ ያለው መልዕክት፣ በተለይ የቴዲ፣ ቅደም ተከተሉን ቢያዛባውም፣ ቁጭ ብላችሁ ተነጋገሩ የሚል ነው። ጥሩ ሃሳብ ነው ሊባል ይችላል፣ ነገር ግን ይህም ቢሆን አልጋ ላይ ተኝቶ እንደማለም ቀላል አይሆንም ። ፖለቲከኞች ቁጭ ብለው የሚነጋገሩት በፍቅር ሳይሆን በሁለት ምክንያቶች ነው። አንዱ፣ አንደኛው ወገን አሸናፊ እየሆነ ሲመጣ እና ሌላኛው ወገን እየተሸነፈ መሆኑ ሲሰማው፣ ሁለተኛው ደግሞ፣ ሁለቱም ሳይሸናነፉ ጉልበታቸውን ሲጨርሱና ሲደክማቸው “እስኪ እርስ በርስ ከምንጠፋፋ እንነጋገርና” ሲሉ ነው። አሁን ባለው ሁኔታ ገዢው ፓርቲ እየተሸነፍኩ ነው ብሎ አያምንም፤ ስለዚህም ተፋቀር ስለተባለ ከልቡ ለድርድር አይቀመጠም፣ ተሸናፊዎችም ጉልበት ሳይኖራቸው የሚያደርጉት ድርድር ዋጋ እንደሌለው ያውቁታልና ከምር አይደራደሩም። በአጭሩ ፍቅር ወደ ድርድር አይወስድም፣ ምናልባት ድርድር ወደ ፍቅር ይወስድ ይሆናል፣ ለመደራደር ደግሞ ስርአት መገንባት አለበት።

አምስተኛ! የፍቅር ያሸንፋል መልዕክት አንዳንዴ አትታገሉ የሚል ድምጸትም አለው። በተለይ ለመብታቸው የሚታገሉ ሰዎችን ፕ/ር ኤፍሬም እንደ ሃይለኛ ወይም በሰከነ- አእምሮ የማይመሩ፣ አድርገው ይቆጠሩዋቸዋል፤ በተዘዋዋሪ መንገድ እንደ በጎች ሆናችሁ አገልግሉ በማለት ስርዓቱ እንዲቀጥልም የሚፈልጉ ይመስላል። ለመብትና ለእኩልነት መታገል እንደ እብደት ካስቆጠረ፣ በእርግጥም ሁላችንም እብዶች ነን፣ ባርነትን እምቢ ብለናልና። ፍቅር ግን ነጻነትን አያወርስም! በነጻ ለመኖር የሚፈልግ ሰው መታገል እንጅ ማፍቀር አይጠበቅበትም።

በቴዲ አፍሮ “የፍቅር ያሸንፋል” መልዕክት ውስጥ አትታገሉ የሚል ድምጸት አለው ባልልም፣ “ፍቅር ፍቅር” የሚለው ስብከት የመታገልን፣ ታግሎ የማሸነፍን ወኔ ይንድብኛል፣ የዚህን ዓለም እውነታ ያፋልስብኛል ። በተደጋጋሚ እንደገለጽኩት በዚህ ዓለም ለመኖር ታግሎ ማሸነፍ ግድ ይላል። በዚህ እና በወዲያኛው አለም መካከል ያለው ልዩነት በምን ይገለጻል ብትሉኝ መልሴ “በትግል ነው” የሚል ነው። በዚህ ዓለም መታገልና ታግሎ መኖር ግዴታና ቅድስ ነው፣ በወዲያኛው ዓለም ደግሞ መታገልና ታግሎ መኖር ግዴታም ቅዱስም አይደለም፣ ማርና ወተት እንደልብ ይፈስበታልና ( ሁለቱንም ለማትወዱ ግን እንጃ! ደግሞም መቼ ሄደህ አየኸው? እንዳትሉኝ)። ለማንኛውም በዚያኛው አለም ትግል የለም፣ ሀብታምና ደሃም የሉም፣ እኔና ቢል ጌት ከአንድ ማዕድ እኩል እንቆርሳለን፣ ስለዚህም ተፋቀሩ የሚለን ሳይኖር እንፋቀራለን። ምንስ የሚጣላን ነገር አለ? በሃብት እንዳንጣላ፣ ሀብት ማፍራት ክልል ነው፣ በሴት እንዳንጣላ ሴት መያዝ ክልል ነው ( ሰማይ ቤት የሚኖረን ጾታም አይታወቅም)፣ ለስልጣን እንዳንጣላ፣ ስልጣን በአንድ አምላክ በሞኖፖል ተይዟል፣ በእግዚአብሄር ላይ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ወይም መፈንቅለ መንግስት እናድርግ ብለን እንዳንነሳ ቀድም ብሎ የሞከረው ሳጥናየልም የተሰጠውን ቅጣት የምናውቀው ነው፤ ታዲያ ለምን አንፋቀር። መማር፣ መውደቅ፣ ማለፍ ምናምን የሚባል ነገር ከሌለ፣ ያለጭንቀት ጧት ተኝተን ማታ ከተነሳን መፋቀርማ ሲያንሰን ነው። እሱን ይጭነቀው እንጅ የእኛማ ስራ ቁጭ ብሎ መቀለብ ነው ( እንዳትወፍሩ ግን ስፖርት መስራት ልመዱ)። ትክክለኛው ፍቅር ያለው ሰማይ ቤት ነው። ቴዲ ወንድሜ፣ ምድር ላይ ትክክለኛውን ፍቅር አገኘዋለሁ ብሎ ባይደክም ይሻለዋል እላለሁ። ምናልባት እሱ አግኝቶት እኔ ሳላገኘሁ ቀርቼም ከሆነ የሚገኝበትን መንገድ ያመላክተኝና ልከተለው።

በመጨረሻም፣ ቴዲ አፍሮ “ፍቅር ያሸንፋል” እያለ ማዜሙን ትቶ “ዲሞክራሲ ያሸንፋል” እያለ ቢያዜም እሱ የሚመኘው መቻቻልና ተከባብሮ መኖር በእሱ እድሜ እውን ይሆናል እላለሁ። ቴዲና አድናቂዎቹ ምን ትሉ ይሆን?


Viewing all articles
Browse latest Browse all 13695

Trending Articles



<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>